ኢትዮጵያን ብሎም አፍሪቃን ለማገልገል የወጣትነት፣ የጎልማሳን ብሎም የዕድሜ ማምሻን መገበር ያውም ያለ ስስት መስጠት ለያኔው ትንታግ ምናሴ እንዲሁም ለምሁሩ እና ጉምቱው የሕግ መምህሩ ምናሴ ኃይሌ የሕይወት ፍልስፍናቸው ነበር፡፡ በታኅሣሥ 24/1922 ዓ.ም ከአባታቸው ከባላምባራስ ኃይሌ ድብነህ እና ከእናታቸው ኢሌኒ ኃይሌ በሐረር ከተማ የተወለዱት ምናሴ ኃይሌ በቀዳማዊ ኃይለስላሴ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚንስትርን ጨምሮ በዲፕሎማትነት እና በበርካታ ኃላፊነቶች አገርን እና ሕዝብን አገልግለዋል፡፡
ከደርግ መንግስት ወደ ስልጣን መምጣት ጋር ተያይዞ ለስደት የተዳረጉት ምናሴ በተለዩ የአሜሪካ ዩኒቨርስቲዎችም በሕግ ትምህርት ክፍል መምህር እና ተመራማሪ በመሆን አገልግለዋል፡፡
ለሃምሳ ዓመታት የሚወዷትን አገራቸውን እንደናፈቁ እና በሩቅ እንዳሰቡ በስደት የኖሩት ምናሴ በተወለዱ በ95 ዓመታቸው በስደት በሚኖሩበት አገረ አሜሪካ ኒው ጀርዚ ግዛት ህልፈታቸው ተሰምቷል፡፡








